ለኢትዮጵያ ስፖርት ሳይንስ ባለሙያዎች ማህበር አባላት የፀረ-አበረታች ቅመሞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ
አዲሰ አበባ፣ መጋቢት 19/2018ዓ.ም.
***
የኢትዮጵያ ስፖርት ሳይንስ ባለሙያዎች ማህበር 4ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በዛሬው ዕለት በተለያዩ ርዕሰ-ጉዳዬች በውይይት እና በስልጠና በመካሄድ ላይ ይገኛል። ጉባኤው በማህበሩና በኢትዮጵያ ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን ትብብር የተዘጋጀ ነው።
ጉባኤውን በንግግር የከፈቱት የማህበሩ የወቅቱ ፕሬዝዳንት አቶ ቢልልኝ መቆያ፣ ባለስልጣን መ/ቤቱ ጉባኤው እንዲካሄድ ላደረገው ትብብር ምስጋናቸውን አቅርበው፣ “የፀረ-አበረታች ቅመሞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናው ዓላማ የስፖርት ሳይንስ ባለሙያዎች የፀረ-አበረታች ቅመሞች ፅንሰ-ሀሳብን በመረዳት በሙያቸው የተሻለ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ታስቦ ነው።” ብለዋል።
ስልጠናው የፀረ-አበረታች ቅመሞች መሠረታዊ ጉዳዬችና አተገባበር በሚል ርዕስ በባለስልጣን መ/ቤቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር በወ/ሮ ፋንታዬ ገዛኸኝ የአበረታች ቅመሞች ጽንሰ-ሀሳብ፣ የህግ ጥሰት ዓይነቶችንና የሚያስከትሉትን ቅጣት፣ የአበረታች ቅመሞች የተፅዕኖ አድማስን በተመለከተ እና የፀረ-አበረታች ቅመሞች እንቅስቃሴ በኢትዬጵያ ለምን አስፈለገ በሚሉ እና ተያያዥ ርዕሰ-ጉዳዮች ዙሪያ ተሰጥቷል።
በስልጠናው ማጠናቀቂያ ከተሳታፊዎች አጠቃላይ በስልጠናው በቀረቡ ጉዳዬች ዙሪያ ጥያቄዎች ተነስተው ውይይት ተደርጎባቸዋል።

